አረሙ ወያኔ በዬትኛውም መስፈርት ኢትዮጵያዊነትን የመቀማት ሞራሉም ሆነ አቅሙም የለውም = በጣም በእርግጠኝነት። ከሥርጉተ ሥላሴ

 

Image

ጥሪው የማህጸን ነበር። ምላሹም የዕትብት ሃዲድነት ነበር።

ጤና ይስጥልኝ ሞገደኛው ተክሌ እንደምን ሰነበትክ? ደህና ነህ ወይ? የብዕር አጣጣልህ እንደ አቤ ቶኬቻው ውብ ስለሆነ ለረጅም ጊዜ እያደንኩ አነባለሁ። ጠረባህንም አክሎ። በጠረባህ ዙሪያ አንድ ቀን የምለው ይኖረኛል …. ዛሬ ግን ልታገሰው ስላልቻልኩት ማለት ፈለግኩ ….. በሦስት ነገሮች ዙሪያ …. እንዲህም እላለሁ …. እኔው ….

ሳውዲ አረብያ ላይ ለደረሰው ውርደት ተጠያቂው አረሙ ወያኔ ነው። የወያኔ ፖሊሲ ነው ለዚህ የትውልድ ፍልሰት በይፋ የፈቀደው። ሙጃው ወያኔ የተመሰረተበት ይህ ነውና። እኛ ጊዜ እዬጠበቀ ወያኔ በሚያፈነዳው ፈንጅ ዙሪያ ጥቃቱን ለመመከት ዕለታዊ ሰልፍ ስለምነደርግ ነው እንጂ የወያኔ መሰረታዊ ፍጥረት ትውልድን ከማፍለስ ላይ በመሆኑ መርዙ የማይነካውና የማያካተው አንዳችም ነገር የለም። ይህ የጥፋት አዟሪት የሚነሳው ኢትዮን ቅኝ ለማደረግ ህልማቸው ካልተሳከ ሀገሮች ምኞት ነው። ስለሆነም ዒላማችን ሊነሳ የሚገባው ከጥንስሱ መሰረት ላይ መሆን አለበት እላለሁ እኔ። ይህን መሰረት ያያዘ የኢትዮጵያዊነት የጥላቻ ፖሊሲ ከሥሩ ለመንቀል ደግሞ ከበቀለበት ማንፌስቶ ነው የትግሉ ወላፈን መነሳት ያለበት የሚል ጠንካራ አድምታ ነው ያለኝ በግሌ። መዳህኒቱም የወያኔ ማንፌስቶ ግብዕተ – መሬት ሲፈጸም ብቻ ነው። የፈውሱ ፍሬ ነገር ከሃርነት ትግራይ ህልፈት ላይ ነው። እያንዳንዱን የወያኔ የጥፋት ሆነ የቅጣት የበቀል እርምጃ በሥርዓት በተጠና ሁኔታ ቢመረመር ቢተነተን – ቢነበብ – ቢፈታታሽ ድርጀቱ ከተፈጠረበት እንቁላል አስኳል ውስጥ ይመነጫል።

ለማንኛውም በሳውዲ ላይ የተሰነዘረብን የጥቃት እርምጃ ለመቃወም እልፎችን ያስቆጣው ሰላማዊ ሰልፎች ወያኔ ኢትዮጵዊነትን የቀማበት ወይንም የነጠቀበት አልነበረም። በጭራሽ።“ኢትዮጵያዊያንን ለማስተባበርና ሳኡዲዎችን ለመጀንጀን የምናቁዋቁመውን ኮሚቴ መለየት ያለብን ይመስለኛል፡፡ሰልፎቹንግንተቀምተናል፡፡ ከልጅ ተክሌ ጹሑፍ የተወሰደ”

ልጅ ተክሌ …. ምን አልባት አንተ በላህበት ሀገር ሆኖ ከሆነ ከተጠያቂዎቹ ውስጡ አንዱ ትሆናለህ። ከማንም በተሻለ ተደማጭነቱም፤ ተቀባይነቱም አለህና! ሁልጊዜ አንተ ታንከባላለህ ድክመቶችን ወደ ሌሎች። …. አንተ እኮ ምርጥ፤ ልዑቅ ከሚባሉ ኢትዮጵውያን ውስጥ አንዱ ነህ። የፖለቲካ ተንታኝ …. በታኝ፤ ጋዜጠኛ፤ አክቲቢስት፤ ሃያሲ፤ የምትፈልገውን ጽፈህ ተከብረህ የሚወጣለህ፤ ያልታገድክ፤ ገድብ ያልተሰረባህ፤ አንቱ የተባልክ ሚሊዮኖች በምታገኘው መድረክ ሁሉ በአክብሮት የሚያዳምጡህ ዕድለኛ ወጣት ነህ …. እና ካናዳ ላይ ወያኔ ኢትዮጵያዊነት ለመቀማት መድረክ ሲያገኝ አንተ የት ነበርክ? ምንስ ትሰራለህ? ….. እራስህን ጠይቅ።

እኔ ሲዊዘርላንድ ነው የምኖረው። ሰላማዊ ሰልፉን ማን እንደጠራው አላወቅም። ከኢሳት ሰምቼ ነበር የሄድኩት። እንዲህ ዓይነት ሰላማዊ ሰልፍ ሲዊዘርላንድ ውስጥ አላዬሁም። እጅግ በጣም ብዙ ሰው ነበር። ቁጭቱ፤ እልሁ፤ እንባው፤ መቃጠሉና መንደዱ … የነጠረው ሰንደቅዓላማ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ካለምንም ቅይጥ በነፍስ ወከፍ ተይዞ ነበር …. እኔ በሰዓቱ እጠረት ነድጃለሁ። ምክንያቱም እዛው ባድርም አልጠግብኩትም ነበርና። ወንድምዓለም ጊዜው ከኖረህ እንዲህ ሰርቸዋለሁ አዳምጠው www.lora.ch.tsegaye ዬ 21.11.2013 ወይንም … በዚህኛው ሊንክም ይቻላል ….

…. ይገርማል። ለመሆኑ ለዛውም ውጭ ሀገር ወያኔ በምን ሞራሉና አቅሙ ነው እኛነታችን፤ ማንነታችን፤ ውስጣችን የመቀማት አቅሙስ ሞራሉስ የሚኖረው። ወንድሜ ሆይ! በአባይ ቦንድ ምን ያህል አረሙ ወያኔ እንዴት እንደ ተራገፈ አላዬህንም? አይታሰብም! ተዎው እኛን ወያኔ ከመጠበት ዘመን ጀምሮ የተወለዱት አዲስ ፈርጦች እኮ ናቸው የኢትዮጵያዊነት መሪና አደራጅ የሆኑት። ይህ ከድንቅ በላይ ነው። ኢትዮጵያዊነት እኮ ገና በሥነ – ምርምር ብዙ የፈካ ተግባር ከፊት ለፊቱ የሚጠብቀው የሰማይ ጥበብ ነው። ተቀማን? አፈርኩልህ ስለቃሉ ….. አኔ የብዕርህ ፍቅረኛ። ጥሎብኝ ደግሞ ድምጽህንም እወደዋለሁ።

ሳውዲ ላይ ለዛውም የውጭ ዜጋ በሳውዲ መሬት ላይ ሰላማዊ ሰልፍ ሲደርግ እኮ ሰማዕት ኢትዮጵያውያኑ የመጀመርያ ናቸው። በማይቻልበት ቦታ ችለው ግን የተሰውበት የተጋድሎ ልዩ ታሪክ …..። የበቀል አምላክ እንደሚበቀለው የሳውዲን መንግስት ቀን ይናገራል …. አምላካችን እንደ ቻይነቱ ቁጡ ነውና።

ሰላማዊ ሰልፉ በመላ ዓለም የኢትዮጵውያን የአትንኩን አኅታዊ ድምጽ … ደመ – ነፍሱን ወያኔን ያራጋፈ፤ ያደናበረ፤ ከእንቅልፉ የቀሰቀሰው፤ ያተራመሰው፤ ከእንሰሳነት፤ ከአራዊትንት አስተሳሰቡ ተግ ብሎ ሰው ስለመሆኑ እራሱን እንዲጠይቅ ያፋጠጠበት፤ ወያኔ ከዛቀጠበት አርንቋ ለመውጣት እፍ ግብ ያለበት በፍጹም ሁኔታ የተዋረደበትና ማንነቱ ያጋለጠበት ነበር ማለት ይቻላል። እውነቱን ልንገረህ ትናንት የተቋቋመው ሰማያዊ ፓርቲ ከወያኔ አስተዳደራዊ ተቋም በላቀ ሁኔታ ዕውቅና ያገኘበት። ኢትዮጵያዊነት የወያኔን የ40 ዓመት ሴራ አክሽፎ የተሞሸረበት – የተመሳጠረበት ታላቅ አብነታዊ የኢትዮጵውያን የወል የጥሪት ውጤት ነበር። ካፒታላችን ቅርሳችን ነው ለዛሬ። ለነገ ደግሞ ትውፊታችን …..

ሌላው አንተ እንዳትቀማ በራስህ ላይ ማተኮር እንዳለብህ የሚያመለክት ነገርም ከጹሑፍ አዬሁ …. እንዳላዬሁ ሆኜ ላላፈው አልፈለግሁም። ምን? ምን አልክ ወንድምዓለም …. „„…የበለጠ የሚያሳስበው ደግሞ፤ ከዚህ ከሳኡዲ ችግር ጋር በተያያዘ ያቁዋቁዋምነው አለማቀፍ ኮሚቴም፤ አስር ሀያ አመት ከምናደርግበት የትግል ስልት ብዙ ፈቀቅ ያለ አይመስልም፡፡ የኮሚቴው ሙሉ ዝርዝር ባይኖረኝም፤ የሶስቱ ሰዎች ስም እንደሚያሳየው ከሆነ፤ ኮሚቴው ዘመኑን ያልዋጀ፤ የአንድ ብሄር ስብስብ ነው የሚመስለው፡፡ ስብስቡ አለማቀፍም አገርአቀፍም ደረጃውን እንዲጠብቅ አልተደረገም፡፡ “ …. „ብንቀበለውም ባንቀበለውም፤ በአደባባይ እንደዚያ ብለን ባናውጅም፤ ይሄንን የሳኡዲን ግፍ ለማለስለስና ለማስቀልበስ የምናቋቁማቸው ተቁዋማትና ስብስቦችም ሁኑ ሌሎች መሰል ፖለቲካዊና ሲቪክ ማህበራቶቻችን፤ በተዘዋዋሪ ይሄንን የሀይማኖትና የብሄር ነባራዊ ሁኔታ ከግምት ያስገቡ መሆን አለባቸው፡፡ ከልጅ ተክሌ ጹሑፍ የተወሰደ” ዬት የት እዬተጓዝክ ነው እናትዬ …. አዬህው በወያኔ የጎጥ ፖሊሲ ምን ያህል እንደ ሰመጥክ፤ እዬተጠቃህም እንደሆነ …. እጅም እንደ ሰጠህ። „እናስተውል“ ይላሉ አባቶቻችን …. እኔ ስለተደራጀው ግብረኃይል እራሱ በነፍሱ ስላለ የሚለውን ይበል ….

ነገር ግን እንደ አንተ ዓይነት ወንድም ግን በብሄረሰብ ስብጥር ላይ ማተኮሩ በጣም መውረድ ነው። ይህ የሚመችህና የሚደላህ ከሆነ ከቶ ስለምን ተሰደደክ? አልገባኝም። የእኔ እናት ጎሰኝነት፤ መንደርተኝነት እኮ ኋላቀርነት ነው። ኋላቀርንት በኢኮኖሚያዊ ስሌቱ ያልተመጣጠነ እድገት ማለት ነው። በአስተሳሰብ ስሌት ስንሄድም ያው ያልተመጣጠነ እድገት ነው …. በ21ኛው ምዕተ ዓመት ከቤተሰብ ቀጥሎ ካላው ጎሳ ላይ መቆም ምን ሊሉት ይቻላል ከኋላቀርነት ውጪ

እባክህ እያንዳንዱን ነገር በዚህ ዝርዝርና ምንዛሬ አታሰባጠረው …. ከዚህ መጠራቅቅ መውጣት አለብህ። አዎና! በአንድ ወቅት አንድ ቅዱስ አባታችን ከዚህዓለም ስደት ላይ እንዳሉ ሲያርፉ ዬእምነት ልዩነት ሳይኖር ሁሉም ኢትዮጵያዊ ቀብር ሥርዓቱ ላይ መገኘቱ ብቻ ሳይሆን ስሜቱን አድንቀህ ተከታታይ ጹሑፎች በኢትዮ ዛሬ ላይ አስነብበህን ነበር። ያን ጊዜ ስትጽፍ ጎሰም አድርገህ የጻፍካት ነበረች። ሊቀ ሊቃውንቱን ብታገኛቸውና ልምዳቸውን ቢያካፍሉህ ግን ሸንቆጥ አድርገህ ያለፍካት ነገር „ላም ባለወለበት መሆኑን ትረዳ በነበረ“ ለማንኛውም ሁላችንም ….. በዚህ ስሌት ከተጓዝን …. ምን አልባት ያን የፍቅር ቤት ደርመሾቹ እኛው ሆነን እናርፋለን። የወያኔን የተጠያቂነት ጠቀረማ ዘመንም የመሸከም ግዴታ ሊኖርብን ነው። በዚህ የፋደሰ መንገድ ከተጓዝን። ከወያኔም እንሻል ቢያንስ እኛ …. በስተቀር ግን ዛሬም ጭቃ ነገም ረግረግ …. መዛገጥ … መዝገጥም – ኪሳራ መከዘን ይሆናል ዕጣ ፈንታችን።

ሌላው ያነሳህው …. እንዲህ ላሉ ድንገተኛ ችግሮች ቋሚ አካላት አለመኖራቸው …. እንዳሳዘንህም ጽፈኃል። አንተ እንዲህ ያለ የቀደመ ሃሳብ ከነበርህ ባለህበት ሀገር ማቋቋም ትችል ነበር አኮ። ማን ጌታ አለብህ። አቅሙ እንዳለህም አስባለሁ። በሌላው ድርጅት ላይ ካለይሉኝታ የምትሰንዝራቸው ወቀሳዎች እዳይደገሙ ጥርት ያለ ብቁ ተቋም። ከስህተት የጸዳ፤ ምርጥ ዘር የሚያፈራ፤ ፍጽምና ሸማው የሆነ ድርጀት የማቋቋም ሙሉ መብት ነበረህ። አለህም። እንዲህ በዬጊዜው እርር ድብን ከምትል …. ልጅ ተክሌ የአንተ ጹሑፍ አምልጦኝ አያውቅም፤ ቃለ ምልልሶችህም ከሌላ ድርጀቶች ጋር አንተ የደረካቸውም ሆነ አንተም በኢሳት ባለህ ቦታ …. ከሌሎች ጋር ያደረከውም …..

እኔ እንደማስበው ወያኔ ብዙ ቢፈታታነውም የኢትዮጵያ ሰብዕዊ መብት አስከባሪ ጉባኤ በፕሮፌሰር መስፍን ይመራ የነበረው፤ እስረኞችን ለመታደግ ውጭ ሀገር የተቋቋመው፤ የአዲሱቱ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ፤ ሌሎቹም … በተጨማሪም በኢሳትም ሰብዕዊ መብት በሚመለከት ራሱን ያቻለ መመሪያ መኖሩ …. ጅምሩ መልካም ነው። በዬጊዜው እስር ቤት የሚማቅቁት ጋዜጠኞች፤ ከዚህም ባለፍ ሥምና ዝና የማይፈልጉ፤ ድምጻቸውን አጥፈተው ከዬሀገሮችም ሆነ በድንበር ዘለልም ከዓለም ዓቀፍ የሰብዕዊ መብት ድርጅቶች ጋር የሚሰሩ ኢትዮጵያውያን እንዳሉም አውቃለሁ። ይደክማሉ። ይሰራሉ።

እኔ በምኖርበት ሲዊዘርላንድ የሰብዕዊ መብት ረገጣ በኢትዮጵያ የቆረቆራቸው ወጣቶች ሶሎቶርን በሚባል ከተማ በ2010 የመሰረቱት አንድ ግብረኃይል አለ። ጥቅምት 12/2012 አቶ ኦባንግ ሜቶ ከአዲሲቱ ኢትዮጵያ የክብር እንግዳ የነበሩበት፤ ከግንቦት 7 ዶር. ታደሰ ብሩ፤ አቶ ወንድምአገኝ ጋሹ ከኢሳት በተገኙበት በዙሪክ የተሳካ ህዝባዊ ስብሰባ

አካሄዶም አይቻለሁ። ስብሰባው ጥሩ መንፈስ ነበረው። ሃሳቦች በሚገባ ተንሸራሽረዋል። ከጀርመን ሙንሽን የመጡ ወገኖችም ነበሩ። …

…. እኔ እንደ አንተ ሃያሲ ስለሆንኩ ከልብ የተደሰትኩበት ስብሰባ ነበር … ማለት እችላለሁ። ያው አልጻፍኩትም። ልመናው ሆነ ድጅ ጥናቱ ገደለኝ። በዬድህረ ገፆች አውጡልኝ በማለት መንከራተት እንጂ …. ያን የመሰለ የወጣቶች ጥረት ወሼኔ ተብሎ በተፃፈለት ነበር። በሌላ የሚዲያ ሽፋን ማግኘቱን ባላውቅም …. እኔ ግን በጸጋዬ ራዲዮ ፕሮግራሜ በዜና ሰርቸዋለሁ ….. ከዚህ ጋር በተያዬዘ መልኩ በሰብዕዊ መብት ዙሪያ ጠንከር ያሉ ተግባራት በሲዊዲንም ተመሳሳይ እንቅስቃሴ እንዳለ ይሰማኛል።

…. በተጨማሪ በዬሀገሩ የሚስማሙ፤ የሚግባቡ፤ የሚደማመጡ ሰዎች የራሳቸውን የግልና የወል ጥረት እንደሚያደርጉም አስባለሁ። ሌላው ቀደም ባላው ጊዜ አዲስ ድምጽና የሲዊዲን እንዲሁም ሌሎች የነፃነት ትግሉ ቤተኛ የሆኑ የኮሚኒቲ ራዲዮኖች ሆነ ማህበራዊ ድሀረ ገፆች በርካታ ተግባራትን ከውነዋል በዚህ ዙሪያ ። እንዲሁም የኢትዮጵውያን የመወያያ ሩሞች የራሳቸውን ሁለገብ ተግባር ሲከውኑ ቆይተዋል። የትኛው የአፍሪካ ሀገር ነው እንደ ኢትዮጵውያን በሀገሩ ጉዳይ ትርጉም ያለው ተግባር ውጭ ሀገር የሚከውነው። እውነት ለመናገር ተጽፎ አያልቅም ….

ልጅ ተክሌ … ችግራችን ከቁጥር በላይ ነው። በሁሉም ቦታ ሁሉም ሊሆን ስላማይቻል ክፍት ቦታ እዬፈለጉ ቀዳዳ መሸፈን የእኔም የአንተም ግዴታ ነው። ሲናሪዮ ሆነ ፕሮቶኮል የማይጠይቁ ብዙ የተግባር መስኮች አሉና። ሌላው ግን እኛም ስደተኞች ነን። ብዙ መከራና ፈተና በግል ህይወታችን እዬፈተለን ነው። ይህም ሆኖ ውጪ ያለነው ኢትዮጵውያን ሁሉንም ሆነናል በአቅማችን ልክ። ከነድክመቶቻችን ለበርካታ ነገሮች በባለቤትነት ስሜት የምንችለውንም አድርገናል እያደረግነም ነው።

ስለሆነም በማናቸው ጊዜ በድንገተኛ የእናት ሀገር የእማ ጥሪ፤ ጠሪም ተጠሪም ወቃሽም ተወቃሽም የለም። ሊኖርም አይገባም። መወቀስ ካለብን ሁላችን። መመስገን ካለብን ደግሞ ሁላችን። ቁስሉም ህምሙም ስቃዩም እኩል ነው። በእናት ሀገር የችግር ቀን የድረሱልኝ ጥሪ አንዱ የክት ሌላው የዘወትር፤ አንዱ ልጅ ሌላው የእንጀራ ልጅ ሊሆን አይችልም …. ከወያኔ በስተቀር …. ወያኔ ይህን ለማጥፋታ 40 ዓመት ቢሰራበትም ንጉሥ ዳዊት በወጣትነቱ ማህልዬን፤ በጎልማሰነቱ ምሳሌን በእርጅና ዘመኑ ደግሞ ሁሉም ኖሮት ዓለምን ፈትሾና አይቶና መርምሮ ከመንፈስ ቅዱስ በተሰጠው መክሊት ከንቱነትን አመሳጠረ …. በሳውዲ የኢትዮጵያዊነት መከራ የወያኔን ከንቱነት ያነበበ፤ የተረጎመና ያመሳጠረ ነበር ዓይንም ህሊናም የለውም እንጂ …. ሙጃው ወያኔ።

እናሳርገው …. በወሳኝ ጉዳይ። …. አንድ ነገር ኢህድግ …. የሚባል ኑሮ ያውቃልን? ከዚህ የወያኔ ሸንኮፍ ተጠቂነትም መውጣት ያለብን ይመስለኛል። የልጅ ተክሌ ጹሑፍ ለወያኔ የጥፋት ሴራ ዕውቅና የሰጠ መሰለኝ። ሀገር ትውልድ ታሪክ ባህል እምነት ያጠፋ ወያኔ ነው። መነሻው መድረሻውም ተልዕኮውም በመሆኑ …. ቅርጽ ነው ኢህድግ ይዘቱ TPLF ነው ትናንትም ዛሬም …. በሌለ ነገር ላይ ምስክርነት …. መስጠት —- ትዝብት ነው … ይበቃኝ። ጨረስኩ።

እኔ እኔ ነኝ የምለው፤ እኔ በእኔ ውስጥ ሳይሾልክ እኔን ሆኖ ሲገኝ ብቻ ነው።

እኔ እኔ ነኝ የምለውም የጠላቴ ዒላማ ተጠቂ አለመሆኔን በፍጹም ሁኔታ በእኔ ውስጥ ሳረጋግጥ ብቻ ይሆናል።

እግዚአብሄር ይስጥልኝ።

Image
ሥርጉተ ሥላሴ

Leave a comment